

ሰላም፤ ቃልኪዳን አበበ እባላለሁ፤ ሁሉንም የቦርድ እና የአባላት ስብሰባዎችን መቆጣጠርና የማህበሩን የአስተዳደር ጉዳዮች በመምራት እሰራለሁ። በኢትዮጵያ የቀድሞ ጠበቃና ዳኛ እንዲሁም በኦታዋ የቅዱስ ተክለ ሀይማኖት ቤተክርስቲያን የቦርድ ሰብሳቢ ሆኜ በማገልገሌ ለዚህ ማህበር አመራር ስራዬ ስኬት እንዳገዘኝ አምናለሁ። ያካበትኩት ልምድ የምንወደውን ማህበረሰብ ፍላጎቶች በማሟላት ረገድ ልዩ ልዩ ክህሎትን እንድጠቀም ረድቶኛል።
ቃልኪዳን አበበ
የቦርድ ሰብሳቢ
አብነት ብዙነህ እባላለሁ፤ የኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር መስራቾች አንዱ ነኝ። በሂሳብ አያያዝ እና በኢኮኖሚክስ የትምህርት ዘርፍ የተመረቅሁ ስሆን በባንክ እና ፋይናንስ የስራ ዘርፍ የብዙ ዓመታት ልምድ ያለኝ በመሆኑ፣ ለማህበሩ ተልእኮ ትርጉም ያለው አስተዋጽዖ ለማድረግ እና አወንታዊ ለውጦችን ለማምጣት እረድቶኛል፡፡ በማህበራችን የቦርድ አባል ሆኜ ስራ የጀመርኩት በኦክቶበር 2018 ሲሆን በፕሮግራም አስተባባሪነት እና በውጪ ግንኙነት የስራ ሀላፊነት ሰርቻለሁ፤ በአሁኑ ወቅትም የፕሮጀክት ፋይናንሺያል ድጋፍን እና የማህበራዊ ሚዲያ መድረክን በማስተባበር ለማህበሩ በምክትል ሰብሳቢነት በፈቃደኝነት እየሰራሁ እገኛለሁ።
በበጎ ፈቃደኝነት የለውጥ ኃይል አምናለሁ፤ በጎ ፈቃደኝነት ለሌሎች መስጠት ብቻ ሳይሆን ጠቃሚ ተሞክሮዎችን ማግኘት፣ ግንኙነቶችን መገንባት እና ማህበረሰብን ማጎልበት ነው። ዘላቂ ተጽእኖዎችን ለሚፈጥሩ ትርጉም ያላቸው ተነሳሽነቶች አስተዋፅዖ ማድረግ ትልቅ ዕድል ነው ብዬ አምናለሁ።

አብነት ብዙነህ
ምክትል ቦርድ ሰብሳቢ

ሰላም፤ ዮዲት ተሰማ እባላለሁ፤ የማህበሩ ገንዘብ ያዥና የፕሮጀክት አስተዳዳሪ ሆኜ እያገለገልሁ እገኛለሁ። ፋይናንሱን በአግባቡ እየተጠቀምንና ማህበራዊ አቅማችንን እያሳደግን መሆናችንን ማረጋገጥ ዋና ሚናዬ ነው። የፕሮጀክት በጀቶችን አዘጋጃለሁ፣ ገንዘቦችን አስተዳድራለሁ እና የሙሉ ዓመት የሂሳብ መዝገቦችን አዘጋጃለሁ። በተጨማሪም ስልታዊ እቅዶችን መንደፍ፣ ከቦርድ አባላትና ከፕሮጀክት ስፖንሰሮች ጋር መስራት፣ ሰራተኛ መቅጠር፣ ማሰልጠን እና መሰል የሰው ሃይል ስራዎችን እሰራለሁ። ሰዎችን መርዳት መቻል መውደዴ የኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር አካል ሆኜ የማገለግልበት ዋና ምክንያት ነው። ያሳደገኝንና አሁን ላለኝ ማንነቴ መሰረት የሆነኝን ማህበረሰብ ማገልገል መቻል የምንጊዜም ህልሜ ስለነበር በስራዬ በጣም ደስተኛ ነኝ።
ዮዲት ተሰማ
የቦርድ የሂሳብ ሀላፊ እና የፕሮጀክቶች አስተዳዳሪ
ሰማነህ ጀመረ እባላለሁ፤ የኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር የቦርድ ፀሀፊ በመሆን እያገለገልኩ እገኛለሁ። ከማህበሩ ፕሬዝዳንት ጋር በመሆን የስብሰባ ቃለ ጉባኤዎችን እመዘግባለሁ። የስብሰባ ማስታወቂያዎችን እና አጀንዳዎችን ደግሞ ለአባላት፣ ለዳይሬክተሮችና ለሌሎች የኮሚቴ አባላት እሰጣለሁ። እንደ ፀሀፊነቴ የማህበረሰቡ ንብረት የሆኑ መፅሃፎችን፣ ደብዳቤዎችን፣ መዝገቦችን፣ ሰነዶችንና ሌሎች መሳሪያዎችን የማደራጀትና የመጠበቅ ሃላፊነት አከናውናለሁ። ከኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር ጋር ማገልገል ከፍተኛ እርካታ ይሰጠኛል። ኢትዮጵያ በነበርኩበት ወቅት ዓለም ዓቅፍና ሀገር አቀፍ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጋር በመስራት ያካበትኩት ሰፊ ልምድ የኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር ውስጥ ላለኝ ሃላፊነት ረድቶኛል። በተጨማሪም በአፍጋኒስታን፣ ፓኪስታን፣ ኢራቅ፣ ኢንዶኔዢያ እና ናሚቢያ ውስጥ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊነት ኦፊሰር በመሆን በመስራቴ በኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር የፀሀፊነት ሚና ብቻ ሳልወሰን የማህበሩ ሁለገብ ንቁ አባል እንድሆን አግዞኛል። የምኖርበትን ማህበረሰብ ማገልገል፤ ችግር ፈቺ ፕሮጀክቶች ላይ መሳተፍና ማስተዳደር በእለት ከለት እንቅስቃሴዎች ላይ ጉልህ ሚና መጫወት ደስታ ይሰጠኛል።

ሰማነህ ጀመረ
የቦርድ ፀሃፊ

የኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር የቦርድ አባል እንደመሆኔ ለተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተግዳሮቶች ተጋላጭ የሆኑ አረጋውያንን ለመርዳት እድል ፈጥሮኛል። እለት ከእለት በማከናውናቸው የማህበሩ ስራዎች በማህበረሰባችን ውስጥ ለሚገኙ አረጋውያን የነበረኝ መረዳትና ለእነዚህ ሰዎች ሊደረጉ የሚገባቸው ድጋፎች በርካታ እንደሆኑ ተረድቻለሁ። በዚህም ምክንያት በህይወታቸው ላይ በእውነት ለውጥ የሚያመጣ ድጋፍ ለመስጠት በማሰብ ፍላጎታቸውን ለመረዳትና ለመርዳት እየሰራሁ እግኛለሁ። ከቦርድ አባልነቴ በተጨማሪ በአባላት ቤት ተገኝቶ በማጫወት ጥሩ ጊዜ እንዲኖራቸው መርዳት እንዲሁም፣ የፍጆታ እቃ ግዢና የመስክ ጉብኝት ዝግጅቶች ላይ በግል በመሳተፍ ሰፊ ጊዜዬን በማህበር ውስጥ አሳልፋለሁ። ከቤተሰቤ እና ከጉዋደኞቼ ጋር በመሆን መልካም ጊዜ ማሳለፍ ያስደስተኛል።
ፋጡማ ሙላው
የቦርድ አባል
አይናለም በጋዜጠኝነት ሙያ የመጀመሪያ ዲግሪ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዲግሪ የካርልተን ዩኒቨርስቲ ምሩቅ ስትሆን ከኢንድያን የመገናኛ ብዙሃን ተቋም ሙያዊ ስልጠናም አግኝታለች። ከሩብ ክፍል ዘመን የበለጠ የጋዜጠኝነት ልምድ ያላት አይናለም
ጽሑፎቿ በጾታ እና በስደት ጉዳዮች ላይ ያተኩራሉ። የኢትዮጵያ ካናዳውያን አዛውንቶች ማህበር ቁርጠኛ አባል እንዲሁም ለማህብሩ የዳይሬክተሮች ቦርድ የፕሮጀክት አማካሪ በመሆን ለማህብሩ ዓላማና ራዕይ መሳካት የበኩሏን እየተወጣች ትገኛለች።

አይናለም ተበጀ
የማህበሩ ፕሮጀክት አማካሪ